🔥 Burn Fat Fast. Discover How! 💪

የቲቪውን ድምጽ ከፍ አረጉላት፡፡ ኢሉአባቦራ በተባለ ከተማ ሕዝባዊ አገልግሎት ስለሚሰጥ አንድ ሆስፒ | ስለ መፅሀፍት በጥቂቱ

የቲቪውን ድምጽ ከፍ አረጉላት፡፡ ኢሉአባቦራ በተባለ ከተማ ሕዝባዊ አገልግሎት ስለሚሰጥ አንድ ሆስፒታል ዶክተሩ ማብራሪያ እየሰጠ ነበር፡፡
እሱ ሲያወራ ግን ቃልኪዳን ተንሰቅስቃ እያለቀሰች ነበር እንጂ የሚለውን እየተከታተለች አልነበረም፤ ‹እሱ ነው፤ እሱ ነው፤ ይሄ ሰውዬ ነው የተሳሳተ ክኒን እንድውጥ አድርጎ ዓይኔን ያሳጣኝ!› አለች፤ በድምፁ ብቻ ለየችው፤ የት እንዳለ የሚነግራት አጥታ ነበር፤ የሠራኸውን እይ ብላ ዓይኖቿን ልታሳየው ሁለት ሶስት ጊዜ ጥቁር አንበሣ ሆስፒታል ሄዳ ነበር፡፡ ግን አላልተገኘም፡፡ አድራሻውን የሚሰጣት ቀርቶ ‹አውቀዋለሁ!› የሚልም አላገኘችም ነበር፡፡ ይኸው፣ ራሱ ድምፁን ይዞ፣ ከነርስነት ወደ ዶክተርነት አድጎ እዚያ ተገኘ፡፡
ድምጹን ከሰማች በሁዋላ ለሦስት ተከታታይ ቀናት ከአልጋዋ አልወረደችም፡፡
ቃልኪዳን፣ ዐይነሥውራን ትምህርት ቤት ገብታ፣ የቀለም ትምሕርቷን በትጋት ቀጥላ፣ የራሷንና የቤተሰቦቿንና የትምሕርት ቤቷን ስም ብታስጠራም፣ ከያዛት ከባድ የራስ ምታት ሕመም ለጊዜው እንድታገግም በማሰብ የሚሰጣትን ሕክምና ለመከታተል ብዙ ዋጋ ያስፈልጋት ነበር፡፡ ሙሉ ለሙሉ ለመዳን ውጪ አገር መሄድ እንዳለባት አንዳንድ ዶክተሮች ቢነግሯትም፣ እሷ ግን ይህን ማድረግ አልችልም ሳትል፣ ብዙ ገንዘብ ያላቸው ሰዎችን ደጅ ጠንታለች፤ እዚህ አገር የሚደረግላት ሕክምና የተሳካ ይሆን ዘንድ፣ እጃቸውን ወደኪሳቸው ከሚሰዱላት ሰዎች መካከል አንዱም አትሌት ሃይሌ ገብረሥላሴ እንደነበር ነግራኛለች፡፡

የደረሰባትን ሁሉ የሰሙ ሰዎች፣ አንዳንዶች የትምህርት ቤት የዓመት ወጪዋን፣ አንዳንዶች የዓመት ቀለቧንና አልባሳቷን ይሸፍኑላት ነበር፡፡ ከእኔ ጋር ስንጨዋወት፣ መልሳ መላልሳ ‹ከጥቁር ሰማይ ስር› ስለተሰኘው መጽሐፌ ያላትን ስሜት ትነግረኝ ነበርና፣ ‹ከፈለግሽ ይህን መጽሐፍ በብሬል ቋንቋ ጽፈሽ፣ አሣታሚ አነጋግረሽ፣ የሚገኘውን ትርፍ ሙሉ ለሙሉ ልትወስጂው ትችያለሽ!› አልኳት፡፡ ደስታዋ ልክ አልነበረውም፡፡ ፋሲካ ሆነች፡፡ ለራሷ የሚጠቅም ብቻ ሳይሆን፣ ለመሰሎቿም ዋጋ ያለው ሥራ እንደሆነ፣ ስሟን በታሪክ መዝገብ ላይ የሚያሰፍር ነገር በመገኘቱ ደስታዋ በዛ፡፡ እዚያው እንደተቀመጥን ስልክ ደዋወለች፤ አሳታሚዎችን አነጋገረች፡፡ ታድዬ! አለች፡፡ እቅዳችን በቀላሉ የሚተገበር መሆኑን ነገረቺኝ፡፡
ቀጥሎ ስለእሷ የሰማሁት በህመሟ ክብደት የተነሣ፣ የሚያስጨንቃት ነገር እንዳትሰራ፣ ሙዚቃ በመስማትና በመጫወት ራሷን እንድታዝናና በሀኪም ትዕዛዝ እንደተሰጣት ነው- ኮሪያ ሆስፒታል ነበር የምትከታተለው፡፡
ትምህርቷን ጨርሣ፣ ዩኒቨርሲቲ ገብታ፣ ከፍተኛ ማዕረግ ስትመረቅ ነበር ይታያት የነበረው፡፡ሆኖም፣‹ተረጋጊ!› አሏት፣ ዶክተሮቹ፡፡ ‹እስከመቼ?› ብላ ጠየቀች፤ ‹ድነሽ እስክትነሽ፤ ጭንቅላትሽ ትምሕርትን ማስተናገድ እስኪችል…›
‹እኔኮ ስማር አልጨናነቅም!› አለች፤ ‹ቢሆንም…› አሏት፡፡ አቋረጠች፡፡
አንድ ቀን፣ ከማኅደረ ጋር የቆጥ የባጡን እያወራንና ዕውቀታችንና ዘመናችን በፈቀደልን ልክ፣ በአገራችን ታሪክና ባሕል ዙርያ እየተወያየን ሳለ፣ ‹እኔ ምልህ መቼ ነው ቃልኪዳንን የማያት? ስለእሷ ሳስብ በጣም ነው ራሴን የምታዘበው?› አልት፡፡ በዝምታና በተመለደች ሀዘን የለበሰች አተያዩ ሲያተኩርብኝ ቆየና፣ ‹‹ለምንድነው ራስህን የምትታዘበው?› አለኝ፡፡
‹ቃል ገብቼላት ነበር፤ አለንልሽ ብያት ነበረ፤ አይዞሽ ወንድም እሆንሻለሁ ዓይነት ተስፋዎች ሰጥቻት ነበር፤ በጣም አፅናንተናት ነበረ፤ ምንም አታድርጉልኝ ግን እየተገናኘን ስለ ሥነጽሑፍ ስለጋዜጠኝነት እናውራ ስትለኝ በፈለግሽው ቀን ደውለሽ ጥሪን ብያት ነበረ፤ ለጊዜው የዘነጋኋቸው ብዙ ቃልኪዳኖች ገብቼላት ነበረ፤ እኔ ግን ጠፋሁባት፤ ዛሬ ነገ ስል ስዘናጋ፣ ይሄው ወራት አለፈ፤ በቃሌ አልተገኘሁም፤ በጣም ነው የማፍረው!› አልኩት፡፡
ዝም አለ፤ ዐይኑን ከዐይኔ ሳይነቅል፡፡
‹እኔም ካገኘኋት ቆይቻለሁ!› አለ በዝግታ፡፡
‹አንተም?!›
‹አዎ፤ አልሞላልህ አለኝ!›
‹ከሚያገኟት ሰዎችስ ትገናኛለህ - ማለቴ እነዚያ የቤት ኪራይና የዓመት ቀለብ ከፍለው ከሚያስተዳድሯት ወዳጆችህ ጋር?›
‹ያገኟታል፤ በጣም ነው የሚያምማት ብለውኛል፤ በጣም ነው የምታሳዝነው፤ ምናልባት ለሕክምና ወደ ውጪ ሀገር ተልካ ይሆናል፤ ወይም ከወላጅ አባቷ ጋር ታርቃ…›
‹ደውዬላት ነበር፤ ግን ስልኳ ዝግ ነው› አልኩት፡፡
‹አዲስ ነገር ካለ ጠይቄ እነግርሃለሁ…›
ሌላ ቀን፣ አራት ኪሎ፣ ምርፋቅ በተባለ ካፌና ሬስቶራንት ውስጥ ቡናችንን እየጣን ሳለ፣ አሁንም ‹ኧረ የዚያች ልጅ ነገር የት ደረሰ?› አልኩት፡፡
‹ለምንድነው አጥብቀህ የጠየቅከኝ?›
‹ቃሌን በልቼ…›

አላስጨረሰኝም፡፡ አንገቱን ደፋ፡፡ የሆነ የሚረብሽ መንፈስ ሰፈረበት፡፡ ‹እንዱ፣ ከወር በፊት ጠይቀኸኝ ነበር፡፡ እንደጠየቅከኝ ወዲያው ስለሚሰማህ የጥፋተኝነት ስሜቶች ነገርከኝ፡፡ እንደዚያ ባለ ስሜት ውስጥ ሆነህ እውነቱን ልነግርህ አልደፈርኩም ነበር!› አለኝ፡፡
‹የተፈጠረ ነገር አለ?›
‹አዎን ቃልኪዳን አርፋለች…›
(ያልተቀበልናቸው ከሚለው መጽሐፌ የተወሰደ)