Get Mystery Box with random crypto!

#የገንዘብ_ታሪክ_በኢትዮጵያ በኢትዮጵያ ገንዘብ አስቀርጸው መገበያየትን የጀመሩት የአክሱም ነገሥታ | ኢትዮጵ

#የገንዘብ_ታሪክ_በኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ ገንዘብ አስቀርጸው መገበያየትን የጀመሩት የአክሱም ነገሥታት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳናል። በላይ ግደይ በ1983 ዓ.ም. ታትሞ በወጣውና ገንዘብ ባንክና መድኀን በኢትዮጵያ በተሰኘ መጽሀፋቸው ላይ በግልጽ እንዳሰፈሩት ከጥንት አክሱማዊያን ነገሥታት መካከል ንጉሥ ኢንደቢስና ንጉሥ አፊላስ የራሳቸውን ህጋዊ ገንዘብ አሳትመው በውጭና በውስጥ በገንዘብ አማካኝነት ይገበያዩ ነበር። ይህም የአክሱማዊያን ስልጣኔ በዘመኑ ምን ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበር ከሚመሰክሩ ጉዳዮች አንደኛው ነው። አክሱም በጊዜው ከነበሩ አራት ታላላቅ ሥልጣኔዎች መካከል አንዷ እንደነበረች ባዕዳን ሳይቀር የመሰከሩት ሀቅ ነው። በዚህም ከፋርስ እስከ ቻይና ከአረቢያ እስከ ሮም የተዘረጋ የውጭ ግንኙነትን አክሱማዊያን መመስረት ችለው ነበር።
ከንጉስ ኢንደቢስና ከንጉሥ አፊላስ ውጪ ብዙ አክሱማዊያን ነገሥታት ገንዘብ አሳትመው እንደነበር ቢታወቅም በዚህ ረገድ ስሙ ጎልቶ የሚነሳውና የሐበሻ ቆስጠንጢኖስ እየተባለ የሚጠራው ገናናው ንጉሥ ኢዛና ነው። የንጉሥ ኢንደቢስና የንጉስ አፊላስ ገንዘቦች በአንደኛው ገጽ የራሳቸው ምስል በገብስና በስንዴ ዛላ ተከበው በሌላው ገጽ ደግሞ የጸሀይና የጨረቃ ምስልና አንዳንዴም አጭር ምሳሌያዊ ንግግር ተቀርጸውባቸው ይገኛሉ። እነኚህ ሳንቲሞች በጥቂቱ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ይገኙ እንጂ አብዛኛዎቹ በውጪው ዓለም ተበትነዋል። በተለይም በኤደን (የመን) ብዙ የአክሱማዊያን ገንዘቦች ይገኛሉ። በላይ ግደይ በመጽሀፋቸው የዚህን ምክንያት ሲያስቀምጡ አክሱማዊያን በጊዜው የምንንም ይገዙ ስለነበር ለወታደር ደሞዝ ሊከፈል የሄደ ገንዘብ ሳይሆን አይቀርም ይላሉ። የንጉሥ ኢዛናን ገንዘብ ስንመለከት ሁለት አይነት ገንዘቦችን እናገኛለን። ንጉሡ ክርስትናን ከመቀበሉ በፊት ያሳተመው ገንዘብ የነበረው ሲሆን ክርስትናን ከተቀበለ በኋላ ደግሞ የመስቀል ምልክትን ያካተተ ገንዘብ አሳትሟል። በዚህም በዓለም የመስቀል ምልክትን በገንዘቡ ላይ ያሳተመ ቀደምት ንጉሥ ለመሆን በቅቷል።
የአክሱማዊያን ስልጣኔ ከጠፋ በኋላ ኢትዮጵያ ዓለምን ረስታ ዓለምም ኢትዮጵያን ረስቶ ዘመናት አልፈዋል። በዚህ መካከል ኢትዮጵያ ገንዘብ አሳትማ ከመገበያየት ስልጣኔ ወርዳ እቃን በእቃ በመለወጥ የግብይት ሂደት ውስጥ ረዥም ዘመናትን ካሳለፈች በኋላ በመካከሉ ማሪያ ትሬዛ ታለር የተባለው የመገበያያ ገንዘብ በጎረቤት ሀገሮች በኩል በነጋዴዎች አማካይነት ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ ዋና የመገበያያ ገንዘብ ሊሆን ቻለ። ይህ ገንዘብ እ.አ.አ. በ1751 ዓ.ም ለኦስትሪያዋ ንግሥት መታሰቢያ የወጣ ገንዘብ ነበር። ይህ ታላቅ ተወዳጅነትን ያተረፈው ገንዘብ በአዋጅ በኢትዮጵያ ገንዘብ እስከተተካበት 1937 ዓ.ም. ድረስ በስፋት ለረዥም ጊዜ ሲያገለግል ቆይቷል።

አጼ ምንሊክ እና አጼ ኃ/ሥላሴ ያወጡት ገንዘብ

አጼ ምንሊክ በዘመናቸው ስላሳተሙት ገንዘብ ባላምባራስ መኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል በዝክረ ነገር መጽሀፋቸው ይህን ብለዋል።

"ከ፲ ፱ ፻ ፩(1901) ፡ ዓ ፡ ም ፡ በፊት ፡ ምንም ፡ ቀደም ፡ ብሎ ፡ በነምሳዋ ፡ ንግ ሥት ፡ በማሪ፡ ቴሬዝ ፡ መልክ ፡ የታተመ ፡ የብር ፡ ገንዘብ ፡ በኢትዮጵያ ፡ ቢታወቅ ፤ አብዛኛው ፡ ሕዝብ ፡ ይሻሻጥና ፡ ይገዛዛ ፡ የነበረው ፡ በጥ ይትና ፡ ባሞሌ ፥ ሸቀጥ ፡ በመለዋወጥ ፡ ነበር ፤ ኋላ ፡ ግን ፡ ዐፄ ፡ ምኒልክ ፡ ባንድ ፡ ንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ መንግሥት ፡ የሚኖር ፡ ሕዝብ ፡ በየጐጡ፡ እንደ ፡ ፈቀደውና ፡ እንደ ፡ ወደደው ፡ መተዳደር ፡ የያዘው ፤ መንግ ሥት ፡ አስቦ ፡ ተፈላጊ ፡ የሆነውን ፡ ባያደራጅለት ፡ ነው ፡ ብለው ፡ ለመ ላው ፡ ሕዝባቸው ፡ አንድነትን ፡ ሰጥቶ ፡ ያስተዳደሩንም ፡ ሥራ ፡ ምቹ ፡ ለማድረግ ፡ በመልካቸውና ፡ በስማቸው ፡ ገንዘብ ፡ አሳትመው ፡ በዚሁም ፡ ሕዝቡ ፡ እንዲገበያይበት ፡ ባ፲ ፱ ፻ ፩(1901) ፡ ዓ ፡ ም ፡ ቀጥሎ ፡ ያለውን ፡ ዐዋጅ ፡ ኣደረጉ ።
በኢትዮጵያ ፡ የመገበያያ ፡ ገንዘብ ፡ ብር ፡ እንዲሆን ፡ የተነገረ ፡
ዐዋጅ ።
ሞአ ፡ አንበሳ ፡ ዘእምነገደ ፡ ይሁዳ ። ምኒልክ ፡ ሥዩመ ፡ እግዚአብሔር ፡
ንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ ዘኢትዮጵያ ። ከዚህ ፡ ቀደም ፡ ነጋዴም ፥ ወታደርም ፡ ባላገርም ፡ የሆንክ ፡ ሰው ፡ ሁለ ፡ በየገበያውና ፡ በየመንገዱ ፡ በስፍራውም ፡ ሁሉ ፡ በጥይት ፡ ስት ገበያይ ፡ ትኖር ፡ ነበር ፤ አሁን ፡ ግን ፡ በኔ ፡ መልክና ፡ ስም ፡ የተሠራ ፡ ብር ፣ አላድ ፣ ሩብ ፣ ትሙን ፤ መሓለቅ ፡ ኣድርጌልኻለሁና ፡ በዚህ ፡ ተገ በያይ ፡ እንጂ ፡ እንግዴህ ፡ በጥይት ፡ መገበያየት ፡ ይቅር ፡ ብያለሁ ፡ የሚሸጥም ፡ ጥይት ፡ ከቤቱ ፡ ያለው ፡ ሰው ፡ ሁሉ ፡ እጅምሩክ ፡ እየወሰደ ፡ ለጅምሩክ ፡ ሹም ፡ ይስጥ ፣ ጥይትም ፡ ለመግዛት ፡ የፈለገው ፡ ሰው ፡ እጅ ምሩክ ፡ እየሄደ ፡ ይግዛው ፤ ይኸንንም ፡ ዐዋጅ ፡ አፍርሶ ፡ ጥይት ፡ ርስ ፡ በራሱ ፡ ሲሻሻጥና ፡ ሲገዛዛ ፡ የተገኘ ፡ ሰው ፤ ገዥውም ፡ ሻጭውም ፡ ስለ ቅጣታቸው ፡ ባ፩(1) ፡ ጥይት ፡ ፩ ፡ ፩ ፡ ብር ፡ ይክፈሉ ፤ ይህነንም ፡ ዐዋጅ ፡ አፍርሶ ፡ ጥይት ፡ ሲሻሻጥ ፡ አግኝቶ ፡ ወደ ፡ ዳኛ ፡ ያመጣ ፡ ሰው ፡ በቅ ጣት ፡ ከሚከፍሉት ፡ ገንዘብ ፡ እኩሌታውን ፡ ሊያዥው ፡ መርቄለታለሁ።
(ኅዳር ፡ ፳ ፪ (22) ፡ ቀን ፡ ፲ ፱ ፻ ፩ (1901) ፡ ዓ፡ ም ፡ እንጦጦ ፡ ከተማ ፡ ተጻፈ ።)
አዲሱ ፡ ገንዘብ ፡ የተሠራው ፡ ከብር ፡ ስለ ፡ ሆነ ፤ በራሱ ፡ ዋጋ ፡ ያ ለው ፡ በመሆኑ፡ ጭምር ፡ በመላው ፡ ግዛታቸው ፡ በፍጥነት ፡ ያለችግር ፡ ታወቀ ። አንድ፡ ብር፡ ሁለት ፡ አላድ ፡ አራት ፡ ሩብ ፡ ስምንት ፡ ትሙን ፡ ዐሥራ ፡ ስድስት ፡ መሐለቅ ፡ ይመነዘራል ።ይኸም፡ ለማንኛቸውም፡ ጕዳይ ፡ በገበያ ፡ ላይ ፡ ለመገበያየት ፡ የተ መቸ ፡ በመሆኑና ፡ ቢያስቀምጡት ፡ ስለማይበላሽ ፥ በሕዝቡ ፡ ዘንድ ፡ በጣም፡ የተወደደና ፡ የተፈለገ ፡ ሆነ ።
ከዚያም ፡ ወዲህ ፡ በን ፡ ነ ፡ ዘውዲቱ ፡ ዘመን ፡ ለመንግሥትም ፡ ለድኻም ፡ የተመቸ ፡ እንዲሆን ፡ በማሰብ ፡ ቤሳ ፡ የተባለ ፡ ከመዳብ ፡ የተ ሠራ ፡ የብር ፡ ፴ ፪ኛ(32ኛ) ፡ ባፄ ፡ ምኒልክ ፡ መልክ ፡ ታተመ ። ቀጥሎም፣ በባንክ ፡ በኩል ፡ በሁለት፣ ባምስት ፤ባሥር፤ ባምሳ፣ባንድ፡ መቶ፤ ባምስ መቶና ፡ ባንድ ፡ ሺሕ፡ ብር ፡ ሒሳብ ፡ የታተመ ፡ ባንክ ፡ ኖት ፡ የተባለ - የገንዘብ ፡ ወረቀት፡ ወጣ ።
ግርማዊ ፡ ቀዳማዊ ፡ ኃይለ ፡ ሥላሴ ፡ የንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ ዘውድ ፡ በጫኑ ፡ ዘመን ፡ ባ፲ ፱ ፻ ፳ ፫(1923) ፡ ዓ ፡ ም ፡ ግን ፡ በጣም ፡ ተሻሽሎ ፡ እንደ ፡ ዓለም ፡ ሕግ ፡ ሁሉ ፡ በሳንቲም ፡ የሚታሰቡ ፡
መቶ ፡ ሳንቲም ፡(አንድ ፡ ብር) ፡
አምሳ ፡ ሳንቲም ፡(አላድ)
ካያ፡አምስት፡ ሳንቲም ፡ (ሩብ)
ዐሥር ፡ ሳንቲም
አምስት ፡ ሳንቲም
አንድ ፡ሳንቲም ኒኬል፡ የሆኑ ፡ ገንዘቦች ፡ በግርማዊነታቸው፡መልክና፡ ስም፡ታትመው ፡ ጠላት፡በኢትዮጵያ፡እገባ፡ ድረስ፡ እስካ፱ ፻ ፳ ፰ ፡ ዓ ፡ ም ፡ ሕዝቡ፡ በደስታ፡ ተቀብሎ ፡ ሲገበያይባቸው : ቈይቷል ።"

ይቀጥላል