2022-04-01 20:23:10
ጥቂት ጊዜ...
___
ሁለት የዜን መነኮሳት ወደ ገዳማቸው ለመድረስ በሚፋጠኑበት አንድ ማምሻ በመንገዳቸው የሚገኝን ወንዝ እየተሻገሩ ሳለ አንዲት ሴት የሚገማሸረው ወራጅ ውሃ ከወዲያ ወዲህ እያላጋት በጎርፉ ላለመወሰድ ሳሩንና አለቱን እየቧጠጠች ስትታገል ያዩዋታል... ሴቲቱ እጃቸውን ብትዋስ ልትድን የምትችል ቢሆንም የሴትን ገላ መንካት በሚከለክለው የዜን ሕግ ምክንያት አልፈዋት ሊሄዱ ሆነ...
___
በዚህ መሃል አንዱ መነኩሴ ከጉዞው ተናጠበና ወደ ወንዙ ዘልሎ ገባ... ሴቲቱንም ተሸክሞ በማውጣት ከወንዙ ዳር አድርሶ አስፈላጊውን እርዳታ አደረገላት... ሴቲቱ በአጸፋው ምስጋና አቀረበች... ባልንጀራው ዳር ቆሞ ሁኔታውን ይታዘባል...
___
ፀሐይ እየጠለቀች ነው... መነኩሴዎቹ ለሰርክ ምለላ ፈጥነው ከገዳማቸው መድረስ ይኖርባቸዋል... እናም ወደዚያው ተፋጠኑ... ብዙ ተጉዘው ከገዳማቸው በር ሲደርሱ አንደኛው መነኩሴ ሴቲቱን ለረዳት ባልንጀራው እንዲህ አለው... "ቅድም ግን ሴቲቱን መንካትህ ልክ ነበር?... እንዴት መነኩሴ ሆነህ ይህን ታደርጋለህ?" ... በዚህ ወቅት ተወቃሹ አስገራሚ ምላሽ ሰጠ... "ልክ ነህ ሴቲቱን ከወንዙ አውጥቻታለሁ... ገላዋንም ነክቻለሁ... ሆኖም እዚያው ወንዙ ዳር ትቻት መጥቻለሁ... አንተ ግን በልብህ እዚህ ድረስ ተሸክመሃታል" አለው... ህም...
___
ወንዙ ዳር ጥለናቸው ልንመጣ ሲገባን እስከ መቃብራችን አፍ ተሸክመናቸው በመጡ ኮተቶች ምክንያት ስንት ዘመን በድንግዝግዝ ተጓዝን?... ከወንዙ ዳር ባልተውነው ቂም ምክንያት ስንቴ ከበደሉ የሚልቅ ህመም ዕድሜ ዘመናችንን በላው?... ስንት ከፍታዎች ላይ ልንገኝ ስንችል... ስንት የስኬት ማማ ልንወጣ ስንችል... በሕብር - በድምር - በጥምር ልንቆም - ባለጋራችንን ድል ልንነሳ ስንችል... ስንቴ እጅ ሰጠን?...
___
የወዳጄን "የአፍታ እንከን" በዕድሜ ልክ በጎነቱ የለወጥኩ ዕለት ታመምኩ... እርሱ ይቅርታ ጠይቆኝ ሰላሙን አግኝቷል... ግና እኔ እርሱን ባሰብኩ - ባየሁት ቁጥር ቁጣዬ እያገረሸ... ቂም እያቃረኝም እያቃቃረኝም እኖራለሁ...
___
መድረሻዬ ሩቅ ቢሆንም በጓዜ ብዛት የነብር ፍጥነቴን በኤሊ ጉዘት ለውጬ እንገታገታለሁ... በመንገዴ በሰረገላቸው ያስቀመጡኝ ነበሩ... ሆኖም አካሌ ከመቀመጫው ሲውል ሸክሜ ከአናቴ አልወረደም ነበር...
___
ወንዙ ጋ እያለሁ ላደርግ እችለው በነበረ ጥቂት ደግነት ብዙ ውድመት ማስቀረት እየቻልኩ በማለፌ ጸጸት እያኘከኝ እልፍ ጸሐይ ጠልቋል... በወቅቱ ባልሰነዘርኳት በጎ ቃል ምክንያት - ብዙ ልቦች ተጎድተዋል... በወቅቱ ባልዘረጋሁት ክንዴ ምክንያት - ብዙ ጎጆዎች ፈርሰዋል... በወቅቱ ባልደፈንኳት ቀዳዳ ምክንያት - ግዙፍ መርከቦች ሰምጠዋል... በወቅቱ ባላከምኳት ቁስል ምክንያት - ሙሉ አካል ተመርዟል...
___
እነሆ ውብ ቃል...
"The time is always right to do the right thing." ~ Martin Luther King
___
ፍቅርን ከመስጠት በላይ ዕዳ አይኑርባችሁ
242 views17:23