2021-08-17 16:34:24
አዋሽ ባንክና እና ዲስከቨር ግሎባል ኔትወርክ የአጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ
******************************
(ነሐሴ 11 ቀን 2013 ዓ.ም አዋሽ ባንክ፣ አዲስ አበባ)
በኢትዮጵያ ከግል ባንክ ውስጥ ፈር ቀዳጅ እና ትርፋማ የሆነው አዋሽ ባንክ እና ዲስከቨር ግሎባል ኔትወርክ የተሰኘውና መቀመጫውን ቺካጎ አሜሪካ ካደረገው በአለም አቀፍ ደረጃ ሶስተኛው ትልቁ የካርድ ክፍያ አገልግሎት ሰጪ ተቋም ጋር አብሮ ለመስራት የሚያስችላቸውን የአጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ፡፡
ስምምነቱ በመላው የኢትዮጵያ የንግድ ማህበረሰብ ዘንድ የአለምአቀፍ ካርዶችን ተቀባይነት ለማሳደግ የሚያስችል ሲሆን የDiscover፣ የDiners Club International፣ የPULSE እና Network Alliance ካርድ ተጠቃሚዎች ከPOS፣ ከኤቲኤሞች እና በኢ-ኮሜርስ ክፍያ ገጾች በኩል ተቀባይነት እንዲኖራቸው የሚያስችል ነው፡፡
የዲስከቨር ግሎባል ኔትዎርክ ካርድ ተጠቃሚዎች ለተለያዩ ጉዳዮች ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ተመራጭ ካርዳቸውን ለመጠቀም ይፈልጋሉ። ለዚህ ደግሞ በአዋሽ ባንክ እና ዲስከቨር ግሎባል ኔትወርክ መካከል የተፈረመው የአጋርነት ስምምነት መፍትሄ ከመሆኑም ባሻገር በኢትዮጵያ የግብይት መጠንን ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው የዲስከቨር ግሎባል ኔትዎርክ ካርድ የአለም አቀፍ ገበያዎች ምክትል ፕሬዚዳንት ማት ስሎዋን ገልጸዋል፡፡
የአዋሽ ባንክ ሆል ሴል ባንኪንግ ቺፍ ኦፊሰር አቶ ታደሰ ገመዳ በበኩላቸው ዲስከቨር ግሎባል ኔትወርክ ከአዋሽ ባንክ ጋር በአጋርነት ለመስራት የመረጠበት ዋነኛው ምክንያት ባንኩ በአገሪቱ ትልቅ የገበያ ድርሻ ያለው በመሆኑና የPSS Switch አብላጫ ባለቤት በመሆኑ ከሌሎች ባንኮች ጋር ለመስራትም ምቹ ሁኔታን ስለሚፈጥርለት ነው ብለዋል፡፡
ከዲስከቨር ግሎባል ኔትወርክ ጋር በአጋርነት መስራታችን ለአካባቢያዊ እና ለአለም አቀፍ ደንበኞች የክፍያ አማራጮችን ለመጨመር እና ለማስፋት ያለንን ቁርጠኝነት ከማንፀባረቁም በላይ ለገቢ ዕድገትም ጉልህ ሚና ይኖረዋል ሲሉም አቶ ታደሰ ተናግረዋል፡፡
ዲስከቨር ግሎባል ኔትዎርክ በብራዚል ፣ በደቡብ ኮሪያ ፣ በናይጄሪያ ፣ በሕንድ እና በቱርክ ውስጥ ከ 20 በላይ የኅብረት አጋር አውታረ መረቦችን በመጠቀም የፋይናንስ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ከ 200 በላይ አገራት እና ግዛቶች ውስጥ ከ 48 ሚሊዮን በላይ በሚሆኑ ነጋዴዎች (Merchants) እና 2 ሚሊዮን በሚሆኑ የኤቲኤም የገንዘብ መቀበያ ቦታዎች ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሲሆን በአለም አቀፍ ደረጃ ከ270 ሚሊዮን በላይ የካርዱ ተጠቃሚዎች አሉት፡፡
1.4K views13:34