🔥 Burn Fat Fast. Discover How! 💪

#ኢትዮጵ #በአባይ_ላይ_የተደረጉ_ውሎች ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ፀጋ የተከበበች ውብ ሀገር ብትሆንም በ | ኢትዮጵ

#ኢትዮጵ
#በአባይ_ላይ_የተደረጉ_ውሎች

ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ፀጋ የተከበበች ውብ ሀገር ብትሆንም በድህነት አዘቅት ውስጥ ተዘፍቃ የምትኖር፤ባደጉ ሀገራት ተረፈ ምርትና የአየር ብክለት ገፈት ቀማሽነት፤በሚጠጣ ንጹህ ውኃ እጥረት ተጠቂነት የምትነሳ ሀገር ነች፡፡ ኢትዮጵያ በመአድን፣ በለም መሬት፣ በእንስሳት፣ በውኃ ኃብት እንዲሁም በሌሎች አላቂና አላቂ ያልሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ባለፀጋ መሆኗን የሚካድ ባይሆንም በተፈጥሮ የታደለችውን ኃብት ጥቅም ላይ ከማዋል ረገድ ግን እምብዛም አይደለችም፡፡ ሜዳዋንና ተራሯን የሚሸፍን የተፈጥሮ ዝናብ እየተቀበለች ይህ ዝናብ አፈሯንና ወርቋን ጠራርጎ በመውሰድ ለጎረቤት ሀገራት ነፃ ስጦታና ችሮታ እንዲሆን ከመፍቀድ ውጪ የልማት መንገዱን አልተገለጠላትም፡፡ ወንዞች በደራሽ ውኃ ተጥለቅልቀው የገበሬ ማሳ የጎርፍ ሲሳይ ሲያደርጉ ማየት ክረምት በመጣ ቁጥር የምንገነዘበው መራራ እውነት ነው፡፡ አባይን የሚያክል ግዙፍ የውሀ ኃብት ከጉሮሮዋ እየፈለቀቁ የራሳቸው ከርሰ ምድር ሲሞሉ ኢትዮጵያ የበይ ተመልካች ሆና መኖሯን ግርምት ይፈጥራል፡፡

ናይል የሚባለው የአለም ረዥሙ ወንዝ ላይ ያለው ውኃ 85%ቱ የኢትዮጵያ ነው፡፡ ይሁንና ከ50% በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ኑሮውን በኩራዝ መብራት ይመራል፡፡ ይህ ክስተት ወገብን ይቆርጣል፡፡ ”ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል” እንዲሉ ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ 5% እንኳን አስተዋፅኦ ሳታደርግ በምስራቅም በምእራብም የዚሁ ወንዝ ብቸኛ አለቃ ነኝ በማለት በሌሎች የናይል ተፋሰስ ሀገራት ላይ የምትሰነዝረው ዛቻና ማስፈራርያ የሚያስገርም ነው፡፡ የናይል ወንዝ ብቸኛ ባለቤት እንደሆነች በመግለፅ አሁናዊ ተጠቃሚነቷን የሚነካ ማንኛውም አይነት እንቅስቃሴ የደም መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ እንደሆነች በተለያዩ አጋጣሚዎች ስትገልፅ መስማት የተለመደ ሆኗል፡፡ ሆኖም ኢትዮጵያ የግብፅ ሽለላና ቀረርቶ ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት በግዛታዊ ክልሏ ውስጥ በሚገኝ በጥቁር አባይ ላይ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ጀምራ ከ70% በላይ ማድረሷን ይታወቃል፡፡ በሌላ በኩል ይህ ግድብ ለግብፅ ራስ ምታት እንደሆነባት፤ኢትዮጵያ የያዘቸውን የልማት መንገድ ለማደናቀፍም ያልፈነቀለችው ድንጋይ እንደሌለ፤በቀጣይም የማትቆፍረው ጉድጓድ እንደማይኖር ኢትዮጵያውያን የምንገነዘበው እውነት ነው፡፡ የናይል ወንዝ በግብፅና በኢትዮጵያ መካከል የፈጠረውን ውጥረት በተለያዩ ወቅቶች የውጭና የሀገር ውስጥ ሚድያዎች ርእሰ ዜና በመሆን የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ቀልብ መሳብ የቻለ፤አሁንም ውጥረቱ በስምምነት ያልተቋጨ ክስተት ሆኖ ቀጥሏል፡፡

#የናይል_ወንዝ_የማን_ነው

ናይል የአለም ረዥሙ ድንበር ተሻጋሪ ወንዝ ሆኖ 11 ተፋሰስ ሀገራትን የሚያቋርጥ ነው፡፡ የወንዙ ላዕላይ ተፋሰስ ሀገራት የሚባሉት ኢትዮጵያ፣ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳና ኬንያ፤የመሀል ተፋሰስ ሀገራት ደቡብ ሱዳን፣ ኤርትራ፣ ሩዋንዳና ብሩንዲ፤የታሕታይ ተፋሰስ ሀገራት ደግሞ ሱዳን እና ግብጽ ናቸው፡፡ የናይል ገባር ወንዞች ነጭ ናይል፣ ሰማያዊ ናይል(አባይ) እና አትባራ ወንዞች ናቸው፡፡ ነጭ አባይ ከታንዛንያ፣ ኡጋንዳና ኬንያ ድንበሮች አካባቢ ከሚገኘው ከቪክቶርያ ሀይቅ ተነስቶ ወደ ናይል ወንዝ የሚቀላቀል ሆኖ 15% አስተዋፅኦ ያደርጋል፡፡ ሰማያዊ ናይል(አባይ) ደግሞ ከጣና ሀይቅ የሚነሳና 70% አካባቢ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ሲሆን አትባራ የተባለው ወንዝ ደግሞ በተከዘና በሰቲት ወንዝ ገባሪነት ከኤርትራ እና ከኢትዮጵያ ተነስቶ በሱዳን በኩል አድርጎ ናይልን የሚቀላቀልና 15% አስተዋጽኦ የሚያደርግ ነው፡፡ ሰማያዊ ናይል(ጥቁር አባይና አትባራ)ከኢትዮጵያ ሉአላዊ ግዛት ተነስተው ኴርቱምን አቋርጠው ግብፅ የሚገቡና 85% የናይል የውሀ ይዘት የሚሽፍኑ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ሰማያዊና ነጭ ናይል በደቡባዊ የሱዳን ክፍል በሚገኘው ኳርቱም አካባቢ ይገናኙና ተያይዘው ወደ ግብፅ ሲና በረሀ በመክነፍ ሜዲትራንያን ባህርን ይቀላቀላሉ፡፡

(( ይቀጥላል))
ጽንሰ ኢትዮጵያ ሐዳስ


#ለማንኛውም ሐሳብ እና አስተያየት
@Yottor_bot
ላይ ያድርሱን።