🔥 Burn Fat Fast. Discover How! 💪

#የ1906_የበልጂየም_እና_የእንግሊዝ_ስምምነት ይህ ስምምነት ግንቦት 09 ቀን 1906 እ.ኤ.አ | ኢትዮጵ

#የ1906_የበልጂየም_እና_የእንግሊዝ_ስምምነት

ይህ ስምምነት ግንቦት 09 ቀን 1906 እ.ኤ.አ በበልጂየም(ኮንጎን በመወከል) እና በእንግሊዝ መካከል የተከናወነ ሆኖ በዚሁ ስምምነት በአንቀፅ 3 ላይ በግልፅ እንደተመለከተው የኮንጎ መንግስት ከሰምሊኪ ወይም ከልሳንጎ ወንዝ ወደ አልበርት ሀይቅ የሚወርደውን ውሀ ከሱዳን መንግስት ጋር አስቀድሞ ሳይስማማ የውሀውን ይዘት የሚቀንስ ስራ እንዳይሰራ ወይም ውሀውን የሚቀንስ ስራ ለመስራት ለማንም ፈቃድ እንዳይሰጥ በዚህ ውል አድርገዋል የሚል ነበር፡፡ ይህ ስምምነት የኮንጎ ህዝብ ከናይል ወንዝ ላይ የመጠቀም መብቱን የሚከለክል፤የሀገሪቱ ብሄራዊ ጥቅምን የሚጎዳ በበልጅየም ፍላጎት ብቻ የተፈረመ ሲሆን የታችኞች ተፋሰስ ሀገራትን ብቻ የሚጠቅም ኢ-ፍትሀዊ ስምምነት በመሆኑ ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም፡፡

#የ1906_የእንግሊዝ_የጣልያንና_የፈረንሳይ_ስምምነት

ይህ ስምምነት በእንግሊዝ፣ ጣልያንና ፈረንሳይ መካከል በሎንደን የተከናወነ የሶስትዮሽ ስምምነት(Tripartite Agreement) ሲሆን በዚሁ ስምምነት አንቀፅ 4(a)ላይ እንደተመለከተው ፍፁም ግዛታዊ አንድነት ላይ በመመስረት የኢትዮጵያ መብትን ገታ በማድረግ በአንድ በኩል፤ጣልያን በሶማሊያና በኤርትራ ላይ ያላትን የቆየ ጥቅምን በማስጠበቅ በሌላ በኩል፤የእንግሊዝና የግብጽ ጥቅም በናይል ወንዝ ለማረጋገጥ ሶስቱም ሀገራት የተስማሙበት ነው፡፡ ይህ ስምምነት ኢትዮጵያ በልአላዊ ግዛቷ ላይ በሚገኝ የውሀ ኃብት እንዳትጠቀም ሙሉ ለሙሉ ያገለላት በመሆኑ በውሀዋ ላይ እንድትገለገል ሊያሰቆማት የሚችል የውጭ ሃይል እንደሌለና ስምምነቱንም በኢትዮጵያ ተቀባይነት እንደማይኖረው በግልፅ ለሀገራቱ አሳውቃለች፡፡

#የ1925_የእንግሊዝና_የጣልያን_ስምምነት
በ1919 እ.ኤ.አ እንግሊዝ በጣና ሀይቅ ላይ ግድብ እንድትሰራ የኢትዮጵያ ይሁንታ እንድታገኝ ጣልያን ድጋፏን የምትሰጥ መሆኗን የሚገልፅ የስምምነት ማእቀፍ በእንግሊዝና በጣልያን መካከል ተከናወነ፡፡ ይህን ስምምነትን ተከትሎ በ1925 እ.ኤ.አ.ግብፅና ሱዳን በነጭና ሰማያዊ ናይል (ጥቁር አባይ) እንዲሁም በሌሎች የናይል ገባሪ ወንዞች ላይ የውሀ ስራዎችን ለመስራት ቅድሚያ መብት እንዳላቸውና ሌሎች ሀገራት የወንዙን የውሀ ይዘት የሚቀንስ ማንኛውም አይነት ስራ እንደማይሰሩ በመግለፅ ጣልያንና እንግሊዝ የማስታወሻ ልውውጥ አደረጉ፡፡ ይህ የደብዳቤ ልውውጥን ኢትዮጵያ እንደማትቀበለው ተቋውሟን ገልፃለች፤ቅሬታዋን በወቅቱ ለነበረው የአለም መንግስታት ድርጅት (League of Nations) አስታውቃለች፡፡

#የ1929_የእንግሊዝ_እና_የግብፅ_ስምምነት

ይህ ስምምነት ሱዳንን እና ሌሎች በእንግሊዝ ስር የነበሩ ቅኝ ተገዢዎችን(ኡጋንዳ፣ ኬንያና ታንዛንያን)በመወከል በእንግሊዝ እና በግብፅ መካከል የተከናወነ ሆኖ የናይል ወንዝ ተፋሰስ ሀገራትን ሊጎናፀፉት የሚገባቸውን ተፈጥሮአዊና ፍትሀዊ የውኃ ኃብት ተጠቃሚነትን እውቅና የማይሰጥ ፍፁም የሁለትዮሽ ስምምነት ነበር፡፡ ይህ ስምምነት ሱዳንን የተወሰነ ድርሻ ብቻ እንዲሰጣት በማድረግ ግብጽና እንግሊዝ ብቻቸውን የናይል ወንዝ ተጠቃሚ እንደሆኑ በተለይም ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ በብቸኝነት የመወሰንና ድምፅን በድምፅ የመሻር ስልጣን(Veto Power)እንደላትና ይህ መብትም ካለምንም ጣልቃ ገብነት የሚቀጥል መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ የግብፅ ፈቃድ ሳይታከልበት በናይልን ሆነ ናይልን በሚገብሩ ወንዞች ላይ ምንም አይነት የመስኖ ሆነ የኤሌክትሪክ ሃይል አገልግሎት ለመስጠት የሚችል ግንባታ በሌሎች ተፋሰስ ሀገራት መከናወን እንደሌለበት ማእቀብ የሚጥል ነበር፡፡
የ1952 የእንግሊዝና የግብፅ ስምምነት(The Owen Falls Agreement)
የኡጋንዳ ቅኝ ገዥ በነበረችው በእንግሊዝና በግብፅ መካከል የተከናወነ ሆኖ የስምምነቱ ይዘትም በአንድ በኩል ኡጋንዳ ለኤሌክትሪክ ሃይል አመንጪነት የሚውል ግድብ ለመገንባት የሚያስችል ህጋዊ መእቀፍ ለማግኘት፤በሌላ በኩል ደግሞ ግብፅ በናይል ላይ የነበራትን የተቆጣጣሪነትና የአለቃነት ስልጣን አስጠብቆ ለማስቀጠል በማለም የተፈፀመ ነበር፡፡ ይኸውም ግብፅ ካልፈቀደች ምንም አይነት ስራ መስራት እንደማይቻል እውቅና ለመስጠት በማሰብ የተከናወነ ይመስላል፡፡

#የ1959_የግብጽና_የሱዳን_ስምምነት
ይህ ስምምነት በዩናይትድ አራብ ሪፓብሊክ ግብጽና በሱዳን ሪፓብሊክ መካከል የተከናወነ ሲሆን የ1929 ስምምነት ተቀጥያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ከፍተኛው የናይል ውኃ የግብጽ እንደሆነ እውቅና የሚሰጥ ስምምነት ነበር፡፡ በዚሁ ስምምነት አንቀጽ 4 ላይ በግልጽ እንደተመለከተው 55.5 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ለግብጽ፣ 18.5 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ለሱዳን በመስጠት ቀሪው 10 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ደግሞ የአከባቢው የኢኮሎጂካዊ ሚዛን ለመጠበቅ ወደ ሰሃራ ምድረ በዳ እንዲተን በመስማማት ኢትዮጵያ በብርጭቆ እንኳን ውኃ የምትቀዳበት መብት ያላገኘችበት አስገራሚ ውል ነበር፡፡ ይህ ስምምነት ሌሎች ተፋሰስ ሀገራትን ያገለለና ፍፁም የሁለትዮሽ ውል ስለነበር በኢትዮጵያ ተቀባይነት እንደሌለው ተደጋግሞ ተገልጿል፡፡

ጽንሰ ኢትዮጵያ ሐዳስ


#ለማንኛውም ሐሳብ እና አስተያየት
@Yottor_bot
ላይ ያድርሱን።